| 11.03.2010 | 15:00 UTC
በሞቃዲሾ ውጊያ የሞቱት ከአርባ በለጡ
የሶማሊያ መንግሥት ወታደሮችና እሥላም ዓማጺያን ሞቃዲሾ ውስጥ በሚያካሂዱት ከባድ ውጊያ የሞቱት ሰዎች ቁጥር ቢያንስ 43 መድረሱ በዛሬው ዕለት ተገለጸ። ውጊያው ትናንት ከቀትር በኋላ የተጀመረው ዓማጺያኑ በሞቃዲሾ ሰሜናዊ ክፍል መንግሥት የሚቆጣጠሯቸውን አካባቢዎች ባጠቁበት ወቅት ነበር። የሞቃዲሾ አንቡላንስ አገልግሎት ሃላፊ አሊ-ሙሰ dpa ለተሰኘው የጀርመን ዜና አገልግሎት እንደገለጹት በትናንቱ ውጊያ ብቻ 23 ሰዎች ሲገደሉ 79 የሚሆኑም ቆስለው ነበር። ተያይዞ እንደተጠቀሰው ከተገደሉት መካከል አብዛኞቹ ሕጻናትን ጨምሮ ሲቪሎች ናቸው። ዋነኛው የሶማሊያ የዓመጽ ቡድን አል-ሻባብ የመንግሥቱን ወታደሮች በአካባቢው ከሚገኝ ሆቴላቸው ማባረሩን ሲያስታውቅ መንግሥት በበኩሉ አባባሉን መሠረተ-ቢስ ብሎታል። በሌላ በኩል ዛሬም ለሁለተኛ ቀን በተፋፋመው ውጊያ ከሃያ የሚበልጡ ሰዎች መገደላቸው ተነግሯል።










